Wednesday 29 April 2020

ኢማም ሐሰን ኢንጃሞ


በአብዱረዛቅ መሐመድ


ሐሰን ኢንጃሞ ምን ያህል እናውቃቸዋለን? ከጀግንነታቸው በተጨማሪ ሲበዛ ሐይማኖተኛ እና ሰብዓዊነት የተላበሱ እንደነበሩስ እናውቃለን?
ሼህ ዑመር ሼህ በሽር (ከ1860-1923 ዓ.ም) በአረብኛ በጻፉትና ሼህ አብደላህ መሐመድ አሊ “ጥሮነ - የኢትዮጵያ ቀደምትና ታላላቅ ዑለማዎች ታሪክ” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ በተረጎሙት መጽሃፍ እንደተገለጸው፥ ሐሰን ኢንጃሞ ከቁመቱ ረዘም ብሎ ቀጠን ያለ፤ ብዙ የማይበላና የማይጠጣ፤ ጥቁር ቢሆንም ቆንጆ ፊት ያለው፤ ጀግናና በዚህ ሙያውም ማንም የማይደርስበት፤ ከጀግኖች ሁሉ ፈረሰኛ የሆነ፤ ከፈረሰኞች ሁሉ ጀግና የነበረ፣ ከፈረሱ ላይ ወርዶ መጋደልን የሚወድ፤ የትም ቢሆን በጀግንነቱ የሚታወቅ፤ ለጦርነት በሄደበት ሁሉ ድልም ተከትላው የምትሄድ፤ ብቻውን ሆኖ እንደ ብዙ የሚቆጠር ስመጥር ጀግና ነበር።
ኢማም ሐሰን ኢንጃሞ በዲኑ ላይ ለስደት የተዳረገ፤ ብዙዎችንም ያስከተለ፤ ሸሪዓ ድል እንዲያደርግ ያስቻለ፤ በበጎ ሕይወት የተሞላ፤ ጥመትን ያስወገደ፤ ኢማምነትን ያወጀና በሰሃባዎች መንገድ የተጓዘ . . . ታላቅ መሪ ሆኖ አልፏል።
ጦርነት በተጋጋመበት ወቅት ከ’ርሱ ወገን የሆነ አጋዥ ያለ የማይመስለው፤ ጠላቶቹን ብቻውን እያጨደ ለመጨረስ ሳንባው የሚከፈት፤ አጋዦቹ ካሉም ከ’ርሱ ጀርባ ሆነው የሚጠለሉበትና ጋሻቸው የሆነ፤ ይህንንና መሰል ባህሪዎችን ተላብሶ ጠላቶቹ ሲመለከቱት ያለ ጦርነት የሚሸነፉለት፤ እርሱና ከ’ርሱ ጋር ያሉት ደግሞ በአሸናፊነት ምርኮዎችን እያፈሱ እንዲመለሱ የሚያደርግ ወደር የሌለው ጀግና ነበር።
ይህም ገጽታውና ባህሪው ከ’ርሱ ጋር የቆየ ሲሆን ከስደቱ በፊት፣ በስደቱ ጊዜና ከስደቱ በኋላም ጠላቶቻቸው የ’ርሱን ድምጽ ከሰሙ ለመጋደልና ከፊቱ ለመቆም ቀርቶ እግራቸው ርዶ ይፈረጥጡ ነበር። አብረውት የሚዘምቱ ሰዎች ምርኮዎችን ለመሰብሰብ በሚራወጡበት ወቅት እንኳ እርሱ ትኩረቱ ለሱ ሳያደርግ የጠላት ፈረሰኞችን በዓይነ-ቁራኛው የሚጠብቅና ካገኛቸውም ብቻውን ገጥሞ የሚጥላቸው፤ የጀግኖች ጀግና እንደነበር በሁሉም ዘንድ ተመስክሮለታል።
ሐሰን ኢንጃሞ ሲበዛ ቸር እንደነበር ይገለጻል። ለዚህ ምሳሌ እንዲሆን አንድ ታሪክ እናንሳ። የቀቤና ሰዎች በከብት ብዛት የታወቁ ቢሆኑም እርሱ ግን ለዚህ አልታደለም ነበር። ምክንያቱም እርሱ ዘንድ የሚመጡ ከብቶች ለሚስኪኖችና ለወታደሮች ስንቅነት ከመታረድ አልያም ለዘማቾች ከመታደል አይድኑምና ነው።
በአንድ ወቅት ከቀቤና ህዝቦች ጋር ዘምቶ በተመለሰበት ጊዜ ለቤተሰቦቹና ለራሱ እንዲያደርጋቸው ተብሎ 30 ከብቶች ተሰጥቶት ነበር። ሼህ ዑመር (ከላይ የጠቀስኩት መጽሃፍ ጸሃፊ) እነዚህን ከብቶች ለማንም እንዳይሰጥ ወይም እንዳያርድ አስምለዉት ነበር። ነገር ግን አስራ አምስት ቀናት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሁሉም ጨርሷቸው ተገኘ።
በአጠቃላይ ሐሰን ኢንጃሞ ለሸሪዓው ተገዢ የሆነ፣ ቁርዓንን በብዛት መቅራት የሚወድ፣ ከዑለማዎች ጋርም በመቀመጥ ብዙ የሚሰማ ነበር። ሐሰን ኢንጃሞ ማለት ግርማ ሞገስ ያለውና በአጋጣሚ ካልሆነ በቀር የማይስቅ፤ ትጥቁን አንድም ቀን ያልፈታና መሳሪያውን ከራሱ የማይለይ፤ በመስጂድ የሰዎች ጥሪ አድራጊ (ሙዓዚን) እና አገልጋይ የሆነ ነበር።
ሐሰን ኢንጃሞ ከልግስናው የተነሳ አባጅፋር ሰጥተዉት ከነበረው ብዙ ብር 4 ሪያል ብቻ ይዞ ተገኘ። የተረፉትንም ሁለቱን ለሼህ ሱለይማን፤ አንዱን ለሼህ ሁሴንና ቀሪ አንዱን ደግሞ ለሼህ አብድሽኩር ሰጥቶ ተገላገለ። አባቱም እንደዚሁ በጀግንነት፣ በፍትሃዊነት፣ በቃል አክባሪነት፣ ድሆችንና ወላጅ አልባዎችን በመርዳት የታወቁ ነበሩ።
ሐሰን ኢንጃሞ ወደ ጅማ ሄዶ ሲመለስ ቃቄ በምትባል ቦታ ላይ ወባ መሰል ህመም ነክቶት ክፉኛ ታመመ፤ ቤቱም ደርሶ አረፈ።

No comments:

Post a Comment